ባል እና ሚስት በጋራ ሲጠቀሙበት የነበረ መሬት ጋብቻው በአንደኛው ተጋቢ ሞት የተቋረጠ ቢሆንም ልላኛው ተጋቢ በልላ ህጋዊ ምክንያት መብቱ እስካልተቋረጠ ድረስ ይዞታው በስሙ ተመዝግቦ ደብተር ለማግኘት እና በይዞታው ለመጠቀም የሚችል ስለመሆኑ፣ ሴቶች መሬትን በመጠቀም፤በማስተላለፍ፤በማስተዳደርና በመቆጣጠር ረገድ ከወንዶች ጋር እኩል መብት ያላቸዉ ስለመሆኑ የኢ.ፍ.ድ.ሪ ሕ/መ አንቀጽ 35/7/፣ የኦሮሚያ እነ ጫሉሜ ሙለታ እና ጫለሽ ቁልበሻ XXXIV መሬት አዋጅ ቁ. 130/99 አንቀጽ 6/3/ እና ደንብ ቁጥር 151/2005 አንቀጽ 15
No summary available.
መስከረም 23 ቀን 2010 ዓ.ም ዳኞች፡- ብርሃኑ አመነው በዕውቀት በላይ እንዳሻው አዳነ ሃይሉ ነጋሽ እትመት አሰፋ አመልካቾች፡ 1ኛ. ጫሉሜ ሙለታ - ቀረቡ 2ኛ. ሶበቄ ሙለታ - ቀረቡ ተጠሪ፡ ጫለሺ ቀልበሳ - ወ/ድንቁጣ ጉተማ ቀረቡ መዝገቡን መርምረን ተከታዩን ፍርድ ሰጥተናል።
በዚህ መዝገብ የቀረበው ክርክር የገጠር መሬት ይዞታ የሚመለከት ነው። በሥር ፍርድ ቤት አመልካቾች ከሳሾች ተጠሪ ተከሳሽ በመሆን ተከራክረዋል። የከሳሾች (አመልካቾች) ክስ ይዘት ባጭሩ የአመልካቾች አባት እና እናት ይዞታ የነበረ የገጠር መሬት የተጠሪ ባለቤት ሟች ቀጄል ሙለታ ከመሞቱ በፊት ከአመልካቾች እናት ጋር በጋራ ይዞ ሲጠቀም የቆየዉን ወንድማቸው ከሞተ በኋላ ተጠሪ ምንም መብት ሳይኖራት ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ ለብቻዋ እየተጠቀመች ስለሆነ ስፋቱ 1.5 ሄክታር የሆነ የገጠር መሬት እንድትለቅ እንዲወስን ዳኝነት ጠይቀዋል። የተጠሪ መልስ ባጭሩ የአመልካቾች አባት ከሞቱ 17 ዓመት በላይ መሆኑን እናታቸውም ከሞቱ 10 ዐመት በላይ ስለሆነው የአመልካቾች ክስ በይርጋ ላቋረጥ እንደሚገባ ይህም ቢታለፍ የአመልካቾች አባት እና እናት ይህንኑ ይዞታቸውን በስጦታ ለተጠሪ ባል ለሟች ቀጄላ ሙለታ አስተላልፈው በዚህ ይዞታ ባልና ሚስት እስከ 2004 ዓ.ም. በጋራ ሲጠቀሙ ቆይተው የተጠሪ ባል ሲሞት በዚህ ይዞታ ላይ ተጠሪ በስሟ የይዞታ ማረጋገጫ አግኝታበት የያዘችው በመሆኑ አመልካቾች መብት የላቸውም በማለት ክሱ ውድቅ እንዲደረግ ተከራክራለች ።
ክርክሩን በመጀመሪያ ደረጃ ያስተናገደው የአምቦ ወረዳ ፍርድ ቤት ይዞታው መሰረቱ የአመልካቾች አባት እና እናት ስለሆነና ሚስት (ተጠሪ) ባሐን መውረስ ስለማትችል ይዞታውን ለአመልካቾች ትልቀቅ ልላውን የጋራ (የባልና ሚስት) ንብረት መካፈል ትችላለች ሲል ውሳኔ ሰጥቷል ።
ተጠሪ በዚህ ውሳኔ ቅር ተሰኝታ ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ያቀረበች ሲሆን የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤትም ግራቀኙን ካከራከረ በኋላ መሬቱ የአመልካች አባት እና እናት መሆኑ መረጋገጡን ጠቅሶ ለተጠሪ ባል ስጦታ ስለመደረጉ ማስረጃ አልቀረበም ሲል የሥር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በከፊል በማሻሻል ሚስት ከባለቤቷ ጋር ስትጠቀም ስለ ቆየች ከዚህ ይዞታ ላይ 1/8 ይገባታል ሲል ወሰኗል።
ተጠሪ ሁለተኛ ይግባኝ ለኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በማቅረቧ ፍርድ ቤቱም ግራ ቀኙን ካከራከረ በኋላ ክርክር የተነሳበት ይዞታ በ1983ዓ.ም የአመልካቾች አባት እና እናት ለተጠሪ ባል በስጦታ ማስተላለፋቸዉ ፤ በ1996 ዓ.ም የተጠሪ ባል መሬቱን በስሙ አስለክቶ ማሰረጃ ማግኘቱንና የተጠሪ ባል ከሞተ በኋላ ይዞታው በተጠሪ ስም ተመዝግቦ የይዞታ ማረጋገጫ የተሰጣት መሆኑን በማስረጃ መረጋገጡን ጠቅሶ ይዞታው የተጠሪና የሟች ባለቤቷ ቀጄላ ሙለታ ሆኗል ሲል የኦሮሚያ የገጠር መሬት አዋጅ ቁጥር 130/99 አንቀጽ 9 እና በደንብ ቁጥር 151/05 አንቀጽ 10 መሰረት ተጠሪ ባለመብት ስለሆነች መሬቱን ልታካፍልም ሆነ ልትለቅ አይገባም በማለት ውሳኔ ሰጥቷል ። አመልካቾች ለኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታ ያቀረቡ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኙም ። ለዚህ ሰበር ችሎት አቤቱታ የቀረበው በዚሁ ላይ ነው።
የአመልካቾች የሰበር ቤቱታ ተመርምሮ ለክርክር ምክንያት የሆነዉ ይዞታ መሬት የአመልካቾች ወላጆች ይዞታ የነበረ እና አመልካቾች ሲጠቀሙበት የነበረ ስለመሆኑ የወረዳው መሬት እና አካበቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ምላሽ በሰጠበት ሁኔታ የክልሉ ጠ/ፍርድ ቤት አመልካቾች ሟች ወንድማቸውን ለመውረስ ያቀረቡት ጥያቄ የለም ወንድማቸውን ለመውረስ የሚያስችል የሕግ መሰረት የለም ማለቱ በአግባቡ መሆን አለመሆኑን ለመመርመር እንዲቻል ተጠሪ መልስ እንድትሰጥ ተደርጓል ።
የተጠሪ መልስ ይዘት ባጭሩ የአመልካቾች እና የተጠሪ ባል የአባት እና የእናታቸውን ይዞታ በ1999 ዓ. ም ድርሻ ድርሻቸውን የተከፋፈሉ መሆኑን ፤ አመልካቾች የሟች ወንድማቸው ድርሻ የሆነ የውርስ ንብረት ለመካፈል ዳኝነት አለመጠየቃቸውን እና የኦሮሚያ ጠ/ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ማስረጃ መዝኖ የሰጠው ፍርድ መሰረታዊ የሕግ ስሕተት የለውም በማለት ተከራክራለች ።
የጉዳዩ አመጣጥ እና የግራቀኙ ክርክር ከላይ ባጭሩ የተመለከተ ሲሆን እኛም አቤቱታ በቀረበበት ዉሳኔ መሰረታዊ የህግ ስሕተት መፈጸም አለመፈጸሙን አግባብነት ካለዉ ሕግ ጋር በማገናዘብ መርመረናል።
ከመዝገቡ መረዳት እንደተቻለዉ አመልካቾች ክስ ያቀረቡት የአባት እናታቸዉ ይዞታ የሆነ እርሻ መሬት ተጠሪ መብት ሳይኖራት ስለያዘች እንድትለቅ እንዲወሰንላቸዉ ነዉ።ተጠሪ በበኩሐ ይህንን መሬት የአመልካቾች አባት እና እናት በስጦታ ለባለቤቷ በመስጠታቸዉ ከባሐ ጋር በስማቸዉ የይዞታ ማረጋገጫ አዉጥተዉ ሲጠቀሙ እንደነበር እና ባለቤቷ ከሞተም በኋላ በስሟ ደብተር ተሰጥቷት እየተጠቀመች መሆኗን ጠቅሳ ተከራክራለች። ይህንን የፍሬነገር ክርክር በማስረጃ የማጣራትና የመመርመር ሥልጣን የተሰጣቸዉ የስር ፍ/ቤቶች የተለያየ ድምዳሜ ላይ የደረሱ ሲሆን ፍሬነገር በማጣራት እና ማስረጃ በመመርመር ረገድ የመጨረሻ ስልጣን የተሰጠዉ የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ክርክር የቀረበበትን ይዞታ የአመልካቾች አባት እና እናት ለተጠሪ ባል በስጦታ ሰጥተዉ ተጠሪ እና ባሐ ለረዥም ዓመታት ሲጠቀሙ መቆየታቸዉን አረጋግጧል።
ስለሆነም አከራካሪዉ ይዞታ ሥረ-መሰረቱ የአመልካቾች አባት እና እናት መሆኑ በአስተዳደር አካል ቢገለጽም ለተጠሪ ባል በስጦታ መተላለፉን የስር ፍ/ቤት በማስረጃ አረጋግጧል ።በዚህ አኳኋን ባልና ሚስት ሲጠቀሙበት የኖሩትን ይዞታ ባል ማለትም የአመልካቾች ወንድም ስለሞተ ተጠሪ የመዉረስ መብት የላትም ሲሉ አመልካቾች ያቀረቡት ክርክር አግባብነት ባለዉ የመሬት አጠቃቀም አዋጅ ሆነ በኢ.ፍ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት መሰረት ተቀባይነት ያለዉ አይደለም ።በኢ.ፍ.ዲ.ሪ. ሕገ መንግሥት ከተረጋገጡት የሴቶች የእኩልነት መብት አንዱ መሬትን በመጠቀም ፤በማስተላለፍ፤በማስተዳደርና በመቆጣጠር ረገድ ከወንዶች ጋር እኩል መብት ያላቸዉ ስለመሆኑ የሚደነግገዉ አንቀፅ 35(7) ነዉ ። ይህንኑ ሕገ መንግስታዊ መብት ለማስፈጸም የወጣዉ የኦሮምያ የገጠር መሬት አዋጅ ቁ/130/99 አንቀጽ 6(13) እና ደንብ ቁ/ 151/05 አንቀጽ 15 ይዘት አንደሚያስገነዝበን ባልና ሚስት በጋራ ሲጠቀሙበት ቆይተዉ ጋብቻቸዉ በአንደኛዉ ተጋቢ ሞት ምክንያት ሲቋረጥ በህይወት ያለዉ ተጋቢ በልላ ሕጋዊ ምክንያት መብቱ ካልተቋረጠ በስተቀር ይዞታዉ በስሙ ተመዝግቦ ደብተር እንደሚሰጠዉና በዚህ ይዞታ መጠቀም መብቱ እንደሚቀጥል ነዉ ።
በተያዘዉ ጉዳይ ቀደም ሲል ይዞታዉ ለተጠሪ ባል በስጦታ ተላልፎ በተጠሪና በባለቤቷ ስም ተመዝግቦ በጋራ ሲጠቀሙበት ቆይተዉ የተጠሪ ባል ሲሞት ከ2000ዓ.ም ጀምሮ በተጠሪ ሰም ተመዝግቦ ተጠሪ እየተጠቀመችበት ስለመሆኑ የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በማስረጃ አረጋግጦ ተጠሪ መሬቱን ልትለቅ አይገባም በማለት የሰጠዉ ዉሳኔ እና ይህንኑ በማጽናት የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የሰጠዉ ትዕዛዝ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ አላገኘንም ። በዚሁ አግባብ ተከታዩን ወስነናል ።
1-የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁ/239515 ላይ በ 02/10/2008 ዓ.ም የሰጠዉ ዉሳኔ እና ሰበር ችሎቱ በመ/ቁ/248943 በ27/03/2009ዓ.ም የሰጠዉ ትዕዛዝ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁ/348(1) መሰረት ጸንቷል ።
2-ክርክሩ ያስከተለዉን ወጪና ኪሳራ ግራቀኙ የየራሳቸዉን ይቻሉ ብለናል ።
No topics extracted.