የዕግድ ትእዛዝ በባህሪው ጊዜያዊ በመሆኑ ለዕግዱ ምክንያት የሆነው ክርክር ዕልባት ሲያገኝ የሚነሳ ስለመሆኑ፣ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 154
No summary available.
መ/ ጥቅምት 20 ቀን 2010 ዓ.ም ዳኞች፡- አልማው ወል ሙስጠፋ አህመድ አብርሃ መሰለ ጳውሎስ አርሺሶ ሰናይት አድነው አመልካች፡- አቶ ፋንታሁን ተፈሪ - ጠበቃ ብርሃኑ ከፍያለው ቀረቡ ተጠሪ፡- ወ/ሮ አበባ ገ/ማርያም - ጠበቆች ጐሣዬ ጉርሙና አለማየሁ ለገሰ ቀረቡ መዝገቡን መርምረን ተከታዩን ፍርድ ተሰጥቷል።
ጉዳዩ ከጊዚያዊ እግድ ትዕዛዝ ጋር የተያያዘ ክርክርን የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረውም በፍድራል መጀመሪያ ፍርድ ቤት ነው።
በሥር ከፍተኛ ፍርድ ቤት አመልካች ከሳሽ ተጠሪ ተከሳሽ በመሆን እየተከራከሩ ሲሆን ለአሁኑ አቤቱታ መነሻ የሆነውን የእግድ ይነሳልኝ ጥያቄ የቀረበው በአሁኑ አመልካች ጠያቂነት ነው። ዋናው ክርክር የጋብቻ ውጤት የሆነውን ንብረት ክፍፍል የሚመለከት ሁኖ ግራ ቀኙ አሉን የሚሐቸውን ንብረቶችን አይነታቸውንና ብዛታቸውን ዘርዝረው የክፍፍል ጥያቄውን አቅርበዋል። የስር ፍርድ ቤትም በግራ ቀኙ የንብረት ክፍፍል ላይ ግራ ቀኙ በሕጉ አግባብ እንዲከራከሩ ከአደረገ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ የግራ ቀኙን የጋራና የግል ንብረት ስለመሆናቸው ግራ ቀኙ የተማመኑባቸውን ንብረቶች በመለየት የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 242 በሚደነግገው አግባብ በእምነታቸው መሰረት ከፊል ዳኝነት ሰጥቷል። ግራ ቀኙ በተካካዱባቸው ልሎች ንብረቶች ላይ ግን ክርክሩ እንዲቀጥል አድርጓል። በግራ ቀኙ እምነት መሰረት ከፊል ፍርድ ያረፈባቸው ንብረቶችም አንድ G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት፣ አንድ ፒካፕ መኪናና አልጋ ሲሆኑ እነዚህ ንብረቶች በሕጉ አግባብ እንዲከፋፈሉም ተብሎ ተወስኗል። በዚህ ውሳኔ መሰረት G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት በሐራጅ የተሸጠ ሲሆን የአሁኗ ተጠሪ ለስር ፍርድ ቤት ጥር 09 ቀን 2008 ዓ/ም ጽፈው ባቀረቡት አቤቱታ በልሎች ንብረቶች ላይ በግራ ቀኙ መካከል የሚካሄደው ክርክር ውጤት ለተጠሪ የሚያስገኝላቸው ጥቅምና መብት ያለ መሆኑን ጠቅሰው የአመልካች ድርሻ የሆነው የቤቱ ሽያጭ ገንዘብ ለአመልካች ሳይከፈል ተከብሮ እንዲቆይላቸው ዳኝነት ጠይቀው የአሁኑ አመልካችም ድርሻቸው ላታገድ የሚችልበት ሕጋዊ ምክንያት የልለ መሆኑን ጠቅሰው ተከራክረዋል። የስር ፍርድ ቤትም የአመልካችን ክርክር ባለመቀበል G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት ከተሸጠበት ገንዘብ ውስጥ ለአመልካች የሚደርሳቸው ገንዘብ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 154 መሰረት ተከብሮ እንዲቆይ የሚደረግበት ሕጋዊ ምክንያት የለም በማለት ትዕዛዝ ሰጥቷል።
በዚህ ትዕዛዝ የአሁኗ ተጠሪ ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለፍድራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙን ክርክር መርምሮ የስር ፍርድ ቤት የሰጠው ትዕዛዝ በመሻር ገንዘቡ ለጊዜው ተከብሮ እንዲቆይ በማለት ፍርድ ሰጥቷል። በዚህ ፍርድ የአሁኑ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለፍድራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙን ክርክር መርምሮ የፍድራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ ሙሉ በሙሉ አፅንቶታል። የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው። የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡- G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት የግራ ቀኙ የጋራ ሃብት ስለመሆኑ ግራ ቀኙ ተማምነው በሕጉ አግባብ እንዲሸጥ ከተደረገ በኃላ የአመልካች ድርሻ ታግዶ እንዲቆይ የሚደረግበት አግባብ የልለ መሆኑን ዘርዝረው መከራከራቸውን የሚያሳይ ነው፡ አቤቱታቸው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ የተደረገ ሲሆን ተጠሪ ቀርበውም ግራ ቀኙ በፅሑፍ እንዲከራከሩ ተደርጎአል።
የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለጸው ሲሆን ይህ ችሎትም ግራ ቀኙ በጽሁፍ ያደረጉት ክርክር ለሰበር አቤቱታ መነሻ ከሆነው ትዕዛዝ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ እንዲሁም ጉዳዩ ለዚህ ችሎት ሲቀርብ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር ብቻ ጉዳዩን በሚከተለው መልኩ መርምሮታል። ጉዳዩ ለዚህ ችሎት ሲቀርብ የተያዘው ጭብጥ መሰረታዊ ይዘቱ፡- ግራ ቀኙ የጋራ ስለመሆኑ ተማምነው በሀራጅ ከተሸጠው ቤት ሽያጭ ገንዘብ ውስጥ የአመልካች ድርሻ ለጊዜው ታግዶ እንዲቆይ የመወሰኑን አግባብነት ለመመርመር የሚል ሆኖ አገኝቶታል።
ከክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው አመልካችና ተጠሪ የጋብቻ ውጤት በሆነው ንብረት ላይ ክርክር ሲያደርጉ አከራካሪው እግድ የተሰጠበት ገንዘብ የተገኘው የግራ ቀኙ መሆኑ አካራካሪ ያልሆነው ቤት በሐራጅ ተሽጦ መሆኑን፣ ግራ ቀኙ በልሎች ንብረቶች ላይ ክርክር ሲያደርጉ ቆይተው የሥር ፍርድ ቤት በ5/5/2009 ዓ/ም በዋለው ችሎት ውሳኔ በመስጠት መዝገቡን የዘጋው መሆኑን፣ የይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የአመልካች ድርሻ የሆነው ገንዘብ ለጊዜው ታግዶ እንዲቆይ በማለት ዳኝነት የሰጠውም ተጠሪ ከአመልካች የሚፈልጉት ገንዘብ ካለ ለአፈጻጸም እንዲያመቻቸው በሚል ሆኖ እግዱ ተግባራዊ የሚሆነው ተጠሪ በአመልካች ላይ ያቀረቡት የገንዘብ ጥያቄ ውሳኔ እስከሚያገኝ ድረስ መሆኑን በመ/ መጋቢት 01 ቀን 2008 ዓ./ም የሰጠው ውሳኔ የተፈፃሚነት ክፍል በግልጽ የሚያሳይ መሆኑን፣ የስር ፍርድ ቤት በአመልካች በተጠሪ መካከል የነበረውን የገንዘብ ክርክር ተመልክቶ እልባት መስጠቱን በመ/ ጥር 05 ቀን 2009 ዓ/ም የተሰጠው ውሳኔ እንደሚያሳይ አመልካች ገልፀው ለአቀረቡት የሰበር ክርክር በተጠሪ የቀረበ ግልጽ ማስተባበያ የልለ መሆኑን ተጠሪ ለዚህ ችሎት የሰጡት የመልስ ማመልከቻ የሚያሳይ መሆኑን፣ የሥር ፍርድ ቤት በገንዘብ ክርክሩ ላይ እልባት የሰጠ ከመሆኑም በላይ በዚህ ውሳኔ በባንኮቹ ውስጥ ይገኛል ተብሎ ከተረጋገጠውና ግራ ቀኙ እኩል እንዲካፈሉ ተብሎ ከተገለጸው ከብር 303,401.06(ሶስት መቶ ሶስት ሺህ አራት መቶ አንድ ብር ከዜሮ ስድስት ሳንቲም) ውጪ ተጠሪ ከአመልካች የሚፈልጉት ገንዘብ ስለመኖሩ የማያሳይ መሆኑን፣ ተጠሪም ከአመልካች የሚፈልጉት ገንዘብ በባንኮች ውስጥ ይገኛል ከተባለው ውጪ ስለመሆኑ በሰበር አቤቱታቸው ካለመግለጻቸውም በተጨማሪ በስር ፍርድ ቤት በተሰጠው የገንዘብ ክርክር ውሳኔ ላይ ቅሬታ ያላቸውና በሕጉ አግባብ ለበላይ ፍርድ ቤት ያቀረቡ መሆኑን ጠቅሰው ያቀረቡት ክርክር የልለ መሆኑን ነው።
በመሰረቱ ዕግድ የሚሰጠው ለክርክሩ መነሻ የሆነው ንብረት የሚጠፋ፣ የሚበላሽ፤
ተከሳሹ ለልላ ሰው አሳልፎ ለመስጠት፣ ለመሸጥ ወይም በልላ ዘንድ በተሰጠ ውሳኔ ንብረቱን ያለአግባብ አዛውሮ ለመስጠት ወይም ለመሸጥ ያቀደ፣ መሆኑ ወይም የባለመብቱ ጥቅም ለመጉዳት ለልላ ሰው አሳልፎ ለመስጠት የሚደረግ እንቅስቃሴ መኖሩን ፍርድ ቤቱ ከተገነዘበ አስፈላጊውን ትዕዛዝ የሚሰጥ ስለመሆኑ ከፍ/ብ/ስ/ስ/ሕ/ቁ.
154 (1) መረዳት ይቻላል። የድንጋጌው መሰረታዊ ዓላማም ዳኝነት እንዲሰጥለት የጠየቀ ወገን በፍርዱ ሂደት ረቺነቱ ቢረጋገጥለት የተሰጠውን ፍርድ ለማስፈፀም ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠርለት ነው ተብሎ ይታሰባል። ከዚህ አንጻር ጉዳዩን ስንመለከተው ተጠሪ ከአመልካች ላይ የሚፈልጉት ገንዘብ ክርክር ተደርጎ እልባት ያገኘ ሲሆን የተጠሪ መብት ያለበት ስለመሆኑ የተረጋገጠው ጥሬ ገንዘብም በባንኮች ያለ መሆኑን በስር ፍርድ ቤት በመ/ በ05/05/2009 ዓ/ም የተሰጠው የውሳኔ ይዘት ያሳያል።
አከራካሪውን እግድ የሰጠው ፍርድ ቤት እግዱ ተግባራዊ እንዲሆን ትእዛዝ የሰጠውም ይኼው የገንዘብ ክርክር በስር ፍርድ ቤት ታይቶ እልባት እስከሚያገኝ ድረስ ስለመሆኑ የውሳኔው ግልባጭ ያሳያል።
በመሆኑም የእግዱ ትዕዛዝ በባህርይው ጊዚያዊ ከመሆኑም በላይ እግዱ እንዲቆይ ምክንያት የሆነው ክርክርም እልባት ያገኘ በመሆኑ G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት ተሽጦ የተገኘው የአመልካች ድርሻ ገንዘብ ተከብሮ የሚቆይበት ሕጋዊ ምክንያት ቀሪ የሆነ መሆኑን አሁን ካለው የግራ ቀኙ የክርክር ሂደትና ደረጃ ተገንዝበናል። ሲጠቃለልም ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች እግዱን የሰጡበት አግባብ ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 154 መሰረታዊ አላማ የሚነቀፍበት አግባብ ያልነበረ ቢሆንም አሁን ክርክሩ ከደረሰበት ደረጃና ከእግዱ ባህርይ አንጻር ሲታይ እግዱ የሚቆይበት አግባብ የልለ በመሆኑ በተለወጠ ምክንያት የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶችን ውሳኔ ማረም ተገቢ ሆኖ ተገኝቷል። በዚህም ተከታዩን ወስነናል።
በፍድራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በኮ/መ/ቁ. 174440 መጋቢት 01 ቀን 2008 ዓ.ም ተሰጥቶ በፍድራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በፍ/ብ/ይ/መ/ቁ. 126988 ጥቅምት 02 ቀን 2009 ዓ/ም የፀናው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል።
G+1 የሆነ መኖሪያ ቤት ተሽጦ ከተገኘው ገንዘብ ውስጥ የአመልካች ድርሻ ታግዶ የሚቆይበት ምክንያት የለም በማለት ወስነናል። ይፃፍ። ሆኖም ተጠሪ የፍ/መ/ደ/ፍ/ቤት በዋናው ጉዳይ ላይ በሰጠው ውሣኔ በስርዓቱ መሰረት የሚያቀርቡት ቅሬታ ካለ የእግድ ጥያቄውን ከማቅረቡ ይህ ውሳኔ አያግዳቸውም ብለናል።
የዚህ ችሎት ክርክር ያስከተለው ውጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸው ይቻሉ ብለናል።
No topics extracted.