በቀድሞ ህግ እንደ ወንጀል የሚቆጠር ድርጊት በአዲሱ ህግ የወንጀል ድርጊት መሆኑ ቀሪ ከሆነ ጉዳዩ በወንጀል የሚታይበት አግባብ ስላለመኖሩ በአዲሱ የገቢዎችና ጉምሩክ አዋጅ መሰረት ከቀረጥ በነፃ በገባ እቃ አላግባብ መገልገል የወንጀል ተጠያቂነት ሳይሆን አስተዳደራዊ ተጠያቂነት ብቻ የሚያስከትል ስለመሆኑ የኢ.ፍ.ድ.ሪ የወንጀል ህግ አንቀፅ 5(3) አዋጅ ቁ.622/2001 አንቀፅ 98(1)(ሀ)(ለ) የጉሙሩክ አዋጅ ቁ.859/2006 አንቀፅ 163(1)(ሀ)(ለ)
No summary available.
የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም.
ዳኞች፡- አልማው ወል ዓላ መሐመድ ተኸላት ይመስል እንዳሻው አዳነ ቀነዓ ቂጠታ አመልካች፡- የኢትዮጲያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዐ/ህግ ማትሪያሲን ተጠሪ፡- አሚኮ/ሽማቾች የህብረት ስራ ማህበር የቀረበ የለም መዝገቡ መርምረን ፍርድ ተከታዩን ፍርድ ሰጥተናል።
ጉዳዩ የወንጀል ክስ ክርክርን የሚመለከት ሲሆን የተጀመረው በአፋር ክልል የገቢርሱ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአሁኑ አመልካች በተጠሪ ላይ ባቀረበው ክስ መነሻነት ነው። አመልካች ያቀረበው ክስ አጭር ይዘትም የአሁኑ ተጠሪ የኢፈደሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 34/1/ እና የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 622/2001 አንቀጽ 98/1/ሀ/ለ/ የተመለከተውን በመተላለፍ ለሱማል ክልል ህዝብ የሚያገለግል የምግብ ሸቀጥ የለውም ምንዛሪ /ፈራኮ ቫሎታ/ ከቀረጥ ነፃ ሆኖ እንዲገባ የተደረገው 400 ኩንታል ስኳር የመመሪያ ቁጥር 25/2002 አንቀጽ 6 እና 7/2/ የተመለከተውን በመተላለፍ ተጠሪ ሆነ ብሎ ህገወጥ ጥቅም ለማግኘት በማሰብ መመሪያው መሰረት ባለስልጣኑ ባዘዘው መሰረትና ቀን ማጓጓዝ ሲገባው ከተመለከት አላማው ውጭ በመገልገል መብቱን ሽፋን በማድረግ በልላ ሰው ይዞታ ስር ለማዋዋል በህገ ወጥ መንገድ ሲዘዋወር በአዋሽ ጉምሩክ ኬላ በመያዙ በፈጸመው ከቀረጥ ነፃ በገባ እቃ አላግባብ መገልገል ወንጀል መከሰሱን የሚያሳይ ነው።
የተጠሪ ድርጅት ወኪል ቀርቦ በሰጠው መልስ ድርጅቱ ወንጀል አለመፈጸሙን፤ በንብረቱ አጓጓዥ ላይ አመልካች ያቀረበው ክስ በብይን ውድቅ ተደርጓል በማለት ተከራክሯል። የስር ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙ ክርክር ከመረመረ በኃላ አመልካች ባቀረበው ክስ ስኳሩን ጭነው ሲሄዱ የተያዙ ሹፍሮች በፍ/መ/ቁ/ 03544 ተከሰው በነፃ እንደተሰናበቱ፤ የአሁኑ ተጠሪ አብሮ ተከሰው የወጣ ባይሆንም ለክርክሩ መነሻ የሆነው ጉዳይ አንቀጽ በመሆኑ ክስ ላቀርብበት አይገባም በማለት የዓቃቤ ህግ /አመልችች ክስ ውድቅ አድርጎታል። የአሁን አመልች በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያቀረበው ይቅባኝ ቅሬታ ተቀባይነት አላገኘም። የአሁኑ የሰበር አቤቱታ ያቀረበውም የስር ፍርድ ቤቶች ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው።
የአመልካች የሰበር አቤቱታ ተመርምሮ በሰበር እንዲታይ በመደረጉ ግራ ቀኙ የጽሁፍ ክርክር አድርጓል። ዐቃቤ ህግ በሰበር አቤቱታው የአሁኑ ተጠሪ ከአሁን በፊት ተከሶ በነፃ አለመሰናበቱን፣ በሹፍሮች ላይ የቀረበው ክስ የኮንትሮ ባንድ ወንጀል ስለመሆኑ በመዘርዘር የስ ር ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲሻር የጠየቀ ሲሆን ተጠሪ በበኩሉ የስር ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲጸና አመልክቷል። የመልስ መልስም ቀርበዋል።
ይህ መዝገብ ከሰ/መ/ቁ/111087 አንፃር እንዲታይ የቀረበ ሲሆን፤ የፍድራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ሰኔ 19 ቀን 2007 ዓ/ም በሰጠው ውሳኔ የኮንትሮባንድ ወንጀል ፈጽመዋል የተባሉት ሹፍሮች በአመልካች የቀረበባችው ክስና ማስረጃ እንዲከላከሉ ትእዛዝ መስጠቱን ተገንዝበናል። በዚህም ክርክሩ በስር በገቢርሱ ከፍተኛ ፍ/ቤት እንዲቀጥል መደረጉን የውሳኔው ግልባጭ ያመላክታል።
የአሁኑ አመልች መዝገቡ በቀጠሮ ላይ በነበረበት ጊዜ ነሀሴ 22 ቀን 2007 ዓ/ም በፃፈው አቤቱታ በዚህ መዝገብ የተያዘው ክርክር በቀድሞ አዋጅ ቁጥር 622/2001 አንቀጽ 98/1/ሀ/ለ/ እንደወንጀል ድርጊት የሚቆጠር ቢሆንም በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 859/2006 አንቀጽ 163 መሰረት ድርጊቱ አስተዳደራዊ ጥፋት ሆኖ ወንጀልነቱ ቀሪ የተደረገ በመሆኑ በኢፍዲሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 5፣3 መሰረት በሰ/መ/ቁ/ 111086 የተጀመረው የወንጀል ክርክር ተቋርጦ በአዋጅ ቁጥር 859/2006 አንቀጽ 163 መሰረት ጉዳዩ በባለስልጣኑ አስተዳደራዊ ውሳኔ እንዲሰጥበት እንዲፈቀድለት ጠይቋል።
ከስር የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለጸው ሲሆን እኛም ጉዳዩን መርምረናል። እንደመረመርነውም የአሁኑ ተጠሪ የተከሰሰበት አዋጅ ቁ/ 622/2001 አንቀጽ 98/1/ሀ/ እና /ለ/ በአዲሱ አዋጅ ቁጥር 859/2006 አንቀጽ 163 መሰረት ወንጀልነቱ ቀሪ ሆነዋል ወይስ አል ሆነም አመልካች በጉዳዩ አስተዳደራዊ ውሳኔ እንዲሰጥ ያቀረበው ጥያቄ በህጉ አግባብ ነው ወይስ አይደለም የሚሉ ጭብጦች ምላሽ የሚያስፈልጋቸው ነጥቦች ሁነው አግኝተናቸዋል።
የመጀመሪያ ጭብጥ በተመለከተ፡- በአዋጅ ቁጥር 622/2001 አንቀጽ 98/1/ሀ/ እና /ለ/ ስር እንደተመለከተው ከቀረጥ ነፃ በገባ እቃ አላአግባብ መገልገል የወንጀል ተጠያቂነት እንደሚያስከትል ነው። በዚህ ጉዳይ ጥፋተኝነቱ የተረጋገጠበት ሰው የእቃው መወረስ እንደተጠበቀ ሆኖ እቃው በገባ ጊዜ ላከፈል ከሚገባው ቀረጥና ታክስ ጋር የሚመጣጠን የገንዘብ መቀጮና ከሶስት አመት እስከ አምስት አመት በሚደርስ እስራት እንደሚያስቀጣ ተመልክቷል።
በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 859/2006 አንቀጽ 163/1/ሀ/ እና /ለ/ ከቀረጥ ነፃ በገባ እቃ ያለአግባብ መገልገል ያለው ተጠያቂነት ቀረጥና ታክስ መክፈሉ እንደተጠበቀ ሆኖ የቀረጥና ታክሱ በመቶ /50%/ የገንዘብ መቀጮ እንደሚያስቀጣ ተደርጓል። በአዲሱ አዋጅ ቁጥር 859/2006 ክፍል ሰባት የጉምሩክ ጥፋቶች እና ቅጣቶች በሚል በምእራፍ አንድ “የጉምሩክ ጥፋቶች እና አስተዳደራዊ ቅጣቶች” በሚል ከአንቀጽ 156 እስከ 165 የተዘረዘሩትን ድርጊቶች በአስተዳደራዊ ቅጣት የሚታዩ ስለመሆናቸው ከድንጋጌዎቹ ይዞት መረዳት ይቻላል። ይህ ከሆነ ደግሞ አመልካች በአቤቱታው እንዳስረዳው ተጠሪ የተከሰሰበት ጉዳይ አስተዳደራዊ ጥፋት ሆኖ ወንጀልነቱ ቀሪ መሆኑ ተረድተናል። በኢፊዲሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 5/3/ መሰረት በቀደሞ ህግ እንደወንጀል የሚቆጠር ድርጊት በአዲሱ ህግ የወንጀል ድርጊት መሆኑ ቀሪ ከሆነ ጉዳይ በሚታይበት ምክንያት አይኖርም። በዚህም ተጠሪ የተከሰሰበት ጉዳይ በአስተዳደራዊ ውሳኔ የሚታይ እንጂ የወንጀል ተጠያቂነት የሚያስከትል አይደለም ብለናል።
ሁለተኛ ጭብጥ በተመለከተ፡- በአዋጅ ቁጥር 859/2006 አንቀጽ 163 መሰረት የተያዘው ጉዳይ በአስተዳደራዊ ውሳኔ የሚታይ ስለመሆኑና የአሁኑ አመልካችም አስተዳደራዊ ውሳኔዎች የማስተላለፍ ስልጣን በዚህ አዋጅ የተሰጠው በመሆኑ የመወሰን ስልጣኑ የተጠበቀ ነው። በዚህም ተከታዩን ወስነናል።
No topics extracted.