No summary available.
መስከረም 21 ቀን 2006 ዓ.ም ዳኞች፡- ተሻገር ገ/ስላሴ አልማው ወል ዓላ መሐመድ ረታ ቶሎሳ ሙስጠፋ አህመድ አመልካች፡- ሃጅ ፈዬ ገመቹ ሄዳኦ ከጠበቃ አቶ በሽር ወያ ጋር ቀረቡ ተጠሪዎች፡- 1.አቶ ዓለሙ በቀለ 9. አቶ ደበል ማርም 2. አቶ ክፍለ ማሪያም ከበደ 10. አቶ ማስረሻ ገ/ሚካኤል ተወካይ አቶ አለሙ በቀለ 3. አቶ አሰፋ ጥላሁን 11 አቶ እንዳለ ጭልቆ 4. አቶ አሰፋ ይመር 12. አቶ ብርሃኑ ዙርጋ እና 5. አቶ ታደሰ ደምሴ 13. አቶ ወርቁ ባሆ 6. አቶ ገስጥ ይነሱ 14. አቶ አባተ በቀለ አቶ ክ/ማሪያም ከበደ ቀረቡ 7. አቶ ንጉሱ ነሲቡ 15 አቶ በየነ አማረ 8. ፶ አለቃ ለማ በየነ ጉዳዩን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፤
ጉዳዩ የቀረበው አመልካች በኦሮሚያ ክልል የአሪሲ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔና የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔ፣ መሰረታዊ የህግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ ይታረምልኝ በማለት ያቀረበውን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው። ጉዳዩ የንግድ ድርጅት ቤት ሽያጭ የሚመለከት ነው። በሥር ፍርድ ቤት ተጠሪዎች ከሳሽ አመልካች ተከሳሽ በመሆን ተከራክረዋል።
የክርክሩ መነሻ ተጠሪዎች በወኪሎቻቸው በኩል በአመልካች (አንደኛ ተከሳሽ) በሥር ፍርድ ቤት ሁለተኛ ተከሳሽ በሆነው አየለ ኃይለስላሴ ላይ ባቀረቡት ክስ ነው። በሥር ፍርድ ቤት ተጠሪዎች በከሳሽነት ቀርበው በአርሲ ዞን በአሰላ ከተማ በቀበል 07 ውስጥ በ4000 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የሚገኝ ሰማኒያ አራት አባላት ያሉት የልብስ ሰፊዎች የህብረት ሥራ ማህበር ንብረት አለ። ይህንን የልብስ ሰፊዎች የህብረት ሥራ ማህበር የማይንቀሳቀስ ንብረትና ግምቱ ከብር 500,000 (አምስት መቶ ሺህ) በላይ የሆነውን ሁለተኛ ተከሳሽ ከማህበሩ አባላት ፈቃድ ውጭ በአነስተኛ ዋጋ ለአንደኛው ተከሳሽ በመሸጥ በከሳሾች ላይ ከፍተኛ ጉዳት አድርሶብናል። ስለዚህ አንደኛ ተከሳሽ ከሁለተኛ ተከሳሽ ጋር 30/09/97 ያደረጉት የንግድ ቤት ሽያጭ ውል እንዲፈርስ ውሳኔ ይሰጥልን በማለት ክስ አቅርበዋል።
አመልካች በአንደኛ ተከሳሽ በመሆን ቀርቦ በክሱ የገለፀውን ንብረት፣ የንብረቱ ባለሀብት ከሆነው የልብስ ሰፊዎች የህብረት ሥራ ማህበር ሕጋዊ ወኪሎች 30/9/1987 ዓ/ም በተፃፈና በውልና ማስረጃ ጽ/ቤት ውል በብር 110,000 (አንድ መቶ አስር ሺህ ብር) ገዝቸዋለሁ አንደኛ ተከሳሽ የማይነቀሳቀሰውን ንብረት ዋጋ የንብረቱ ባለሃብት ለሆነው የልብስ ሰፊዎች የህብረት ሥራ ማህበር ሙሉ በሙሉ በመክፈል የማይነቀሳቀሰው ንብረት በስሜ አዛውሬአለሁ። የንብረቱም ባለኃብት አንደኛ ተከሳሽ መሆኑን የሚያረጋግጥ ካርታና ፕላን በአስተዳደሩ ክፍል ተዘጋጅቶ ተሰጥቶኛል። ስለዚህ ውሉ ላፈርስ የሚችልበት ምክንያት የለም በማለት ተከራክሯል።
የሥር ፍ/ቤት የግራ ቀኙን ክርክርና ማስረጃ ከሰማና ከመረመረ በኋላ ከሳሾች የማህበሩ አባላት ናቸው።
የአከራካሪው ንብረት ባለሃብት የሆነው የልብስ ሰፊዎች የህብረት ስራ ማህበር ሰማኒያ አራት አባላት እንደነበሩት ተረጋግጧል። ከሰማኒያ አራቱ አባላት ንብረቱን እንዲሸጡ ለሁለተኛው ተከሳሽና ለልሎች ሶስት ማህበሩ አመራር አባላት የውክልና ሥልጣን የሰጡት ሰላሳ አምስት አባላት ብቻ ናቸው።
የማይነቀሳቀሰውን ንብረት የአባላቱ ያልተከፋፈለ የጋራ ሀብት የሚቆጠር በመሆኑ ንብረቱ ለመሸጥ የሁሉም አባላት ሥምምነት አስፈላጊ ነው። የንብረቱም ግምት (ሁለት መቶ ሺ አራት መቶ ሃምሳ ብር) እንደሆነ በባለሙያዎች ተገምቶ ቀርቧል። ስለዚህ ውሉ ፈርሶ - ተዋዋዮች ወደ ነበሩበት ይመለሱ በማለት ውሳኔ ሰጥቷል። ይህ ውሳኔ በኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎትና የሰበር ችሎት ጸንቷል።
ተጠሪዎች በ2/7/2005 ዓ/ም በተፃፈ መልስ የማህበሩ አባላት በማህበሩ ውስጥ ያላቸው መብት እኩል ነው። ማህበሩ 84 አባላት ያለው ሆኖ እያለ ከሰላሳ ዘጠኝ የማይበልጡ አባላት ብቻ ባስተላለፉት ውሳኔና በሰጡት ውክልና አመልካች ቤቱን መግዛታቸው ውሉን የጸና አያደርገውም። ስለሆነ የሥር ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሣኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የለበትም በማለት ተከራክረዋል።
አመልካች ከማህበሩ አባላት 50 ፐርሰንት በላይ ተገኝተውና ምልዕተ ጉባኤ ተሟልቶ በተሰጠው ውሣኔ ገዝቻለሁ በማለት ያቀረበው ክርክር ተገቢነት የልለው ነው። የበታች ፍርድ ቤቶች በፍታብሕር ሕጉ ስለ ጋራ ንብረት የተደነገጉትን መሰረት በማድረግ መወሰናቸው ተገቢና መሰረትዊ የሕግ ስህተት የልለበት ነው። ስለዚህ የአመልካቾችን የሰበር አቤቱታ ውድቅ በማድረግ እንድስናበት በማለት ተከራክሯል።
አመልካች በ7/08/2005 ዓ/ም የተጻፈ የመልስ መልስ አቅርቧል።
ከሥር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር የቀረበው ክርክር ከላይ የተገለጸው ሲሆን እኛም በታች ፍርድ ቤቶች አመልካች ቤቱን ለመግዛት የተዋዋለው ውል ፈራሸ ነው በማለት የሰጡት ውሣኔ የሕግ መሰረትና ድጋፍ ያለው ነው ወይስ አይደለም? የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምረናል።
ጉዳዩን እንደመረመርነው አመልካች አሰላ ከተማ ሸማኔዎች አገልግሎት የህብረት ሥራ ማህበር፣ በአሰላ ከተማ ከፍተኛ ቀበል 07 የሚገኘውን ድርጅት ቤት የገዙት አቶ ተስፋዬ በሻህ (የማህበሩ ላቀመንበር) አቶ ሲሳይ ጅራቱ የማህበሩ ፀኃፊ አቶ አየለ ኃይለ ስላሴ እና አቶ ኃይለማሪያም ደምሴ የተባሉት የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ (ስራ አስኪያጅ) ኮሚቴ አባላት በተገኙበት ልሎች የማህበሩ ሰላሳ አምስት አባላት ማህበሩ መንግስት ግብርና የዘበኛ ደመዎዝ ለመክፈል ባለመቻሉ ንብረቱን ከላይ ስማቸው የተጠቀሰው አራቱ የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ (ስራ አስኪያጅ) ኮሚቴ አባላት ንብረቱን ለአመልካች በብር 110,000 / አንድ መቶ አስር ሺ ብር / በመሸጥ ገንዘቡን እንዲቀበሉ ግንቦት 29 ቀን 1987 ዓ.ም የሰጡትን ውሳኔ እና የውክልና ስልጣን በመመልከት ነው ።
አቶ ተስፍዬ በሻ (የማህበሩ ላቀመንበር) ፣ አቶ ሲሳይ ጅራቱ የማህበሩ ፀኃፊ አቶ አየለ ኃ/ለስላሴ እና አቶ ኃ/ማሪያም ደምሴ የተባሉት የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ (ስራ አስኪያጅ) ኮሚቴ አባላት እነሱን ጨምሮ ሰላሳ ዘጠኝ የማህበሩ አባላት ግንቦት 29 ቀን 1987 ዓ.ም ባስተላለፋት ውሳኔ እና በሰጧቸው ውክልና ስልጣን መሰረት የአሰላ ከተማ ሸማኔዎች አገልግሎት የህብረት ስራ ማህበርን በመወከል ግንቦት 3ዐ ቀን 1987 ዓ.ም አከራካሪውን የማህበሩን ንብረት አመልካች በሽያጭ አስተላልፈዋል። የሽያጭ ውሉን በወቅቱ የውልና ምዝገባ አገልግሎት የመስጠት ስልጣን በነበረው አርሲ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውልና ምዝገባ ክፍል ቀርቦ ተመዝግቧል። የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ (ስራ አስኪያጅ) ኮሚቴ አባላት ቤቱን ለአመልካች የሸጡት ማህበሩን በመወከል ፣ በማህበሩ ስምና /የአሰላ ሸማኔዎች ሁለገብ የህብረት ስራ ማህበር ጽ/ቤት/ የሚል የማህበሩን ማህተም በመጠቀም ነው። በአጠቃላይ ሲታይ የሽያጭ ውሉ የተደረገው የአሰላ ሸማኔዎች ሁለገብ የህብረት ስራ ማህበር እና በአመልካች መካከል ነው።
የህብረት ስራ ማህበራት የራሳቸው የሆነ ልዩ አላማ ያላቸው ፣ የራሳቸው ባህሪያትና ሕጋዊ ሕልውና ያላቸው ናቸው ። እያንዳንዱ አባል በማህበሩ ውስጥ ያለው መብትና ግድታ የሕብረት ስራ ማህበራት አዋጅ ፣የሕብረት ስራ ማህበራት አዋጅን ለማስፈፀም በወጣው ደንብና በማህበሩ መተዳደሪያ ደንብ የሚወሰን ነው።
ተጠሪዎች የማህበሩ አባላት ሰማኒያ አራት ናቸው በማለት የሚከራከሩ ቢሆንም ቤቱ ሲሸጥ ማህበሩ ሰማኒያ አራት አባላት የነበረው መሆኑን የማስረዳት ግድታቸውን እንዳልተወጡ ከበታች ፍርድ ቤቶች ውሳኔ ይዘት ተገንዝበናል። ከዚህ በተጨማሪ ማህበሩ ቤቱ እንዲሸጥ ውሳኔ ሲያስተላልፍ ያልነበሩ ልሎች አባላት አሉ ቢባለ እንኳን ተጠሪዎች ልሎቹም አባላት ወክለው ክስ ማቅረብ ስልጣን የላቸውም።
1ዐ. የሕብረት ስራ ማህበራት ንብረት ላይ መወሰን የሚችለው የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ እንደሆነ በአዋጅ ቁጥር 147/1991 አንቀፀ 21 የተደነገገ ሲሆን የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ ከማህበሩ አባላት ከግማሽ በላይ ሲገኙ እንደሚካሄድ በደንቡ ቁጥር 106/1996 አንቀጽ 20/2/ የተደነገገ ሲሆን ውሳኔ የሚተላለፈው በድምጽ ብልጫ መሆኑ በደንቡ አንቀጽ 23 ተደንግጓል። አመልካች ያአሰላ ሸማኔዎች ሁለገብ የሕብረት ስራ ማህበር ሰላሳ ዘጠኝ አባላት ያስተላለፉትን ውሳኔና የሰጡትን ውክልና በማየት ቤቱን ገዝተዋል። ተጠሪዎች ይህንን የሚያስተባብል ማስረጃ ያላቀረቡ ስለመሆኑ የስር ፍርድ ቤት ውሳኔ ያሳያል። ተጠሪዎች የሚከራከሩት የማህበሩ ንብረት እንደ አባላቱ የጋራ ሀብት ላቆጠርና ንብረቱን ለመሸጥ ሁሉም አባላት ስምምነት በፍታብሕር ሕግ ቁጥር 1266 መሰረት አስፈላጊ ነው በማለት ነው። ይህ የአመልካቾች ክርክር በአዋጅ ቁጥር 147/1991 አንቀጽ 32፣ አንቀጽ 18 ፣ አንቀጽ 19 እና ደንብ ቁጥር 106/1996 አንቀጽ 20 እና አንቀጽ 23 የሚጥስና የሕግ መሰረት የልለው ነው ።
በኦሮሚያ ክልል የአርሲ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔ ፣ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔና የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ የሰጠው ውሳኔ ተሽሯል ።
በአሰላ ሸማኔዎች ሁለገብ የሕብረት ስራ ማህበርና በአመልካች መካከል ግንቦት 30 ቀን 1987 ዓ.ም የተደረገው የቤት ሽያጭ ውል የሚፈርስበት ሕጋዊ ምክንያት የለም በማለት ወስነናል።
ይህ ውሳኔ ተጠሪዎች ከቤቱ ሽያጭ የሚደርሳቸው ድርሻ ካለ የአሰላ ሸማኔዎች ሁለገብ የሕብረት ስራ ማህበርን ወይም ገንዘቡን ተካፍለው ወሰዱ የተባሉ አባላትን ከመጠየቅ የሚገድባቸው አይደለም በማለት ወስነናል ።
በዚህ ችሎት ያወጡትን ወጭና ኪሳራ ግራ ቀኙ ለየራሳቸው ይቻሉ በማለት ወስነናል።
መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ።
No topics extracted.